Episode Synopsis "ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴ፤ አጭር የሕይወቱና የጽሑፉ ታሪክ ሲመረቅ ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ ያሰሙት ንግግር "
"ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴ፤ አጭር የሕይወቱና የጽሑፉ ታሪክ" የተባለው መጽሐፍ ከሰባት አመታት በፊት በብሔራዊ ቲያትር ሲመረቅ ጸሐፊው ዮሐንስ አድማሱ እና ወንድማቸው እና አሰናኙ ዮናስ አድማሱ (ዶክተር) በሕይወት አልነበሩም። የታሪኩ ባለቤት ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴም ቢሆኑ ሕይወታቸው ካለፈ ረዥም አመታት ተቆጥረዋል። ዮፍታሔ ንጉሴ አርበኛ ፣ ባለቅኔ እና የቲያትር ባለሙያ ነበሩ። በ1887 ዓ.ም. በጎጃም ደብረ ወርቅ ተወልደው ደብረ ኤልያስ ዜማ እና ቅኔ የተማሩት ዮፍታሔ የአሮጌው ሥርዓት ሰው ቢሆኑም አብዮተኛው እና ኮምዩኒስቱ ዮሐንስ ቀርቦ እንዲያጠናቸው እንዲመረምራቸው የሚያደርግ ተክለ ስብዕና ነበራቸው። የሕይወት ታሪካቸው እና ሥራዎቻቸው ላይ ያተኮረው ይኸው መጽሐፍ ተጀምሮ ለሕትመት እስኪበቃ ከአራት አስርት አመታት በላይ ወስዷል። ዮሐንስ የጀመረውን ያጠናቀቁት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የነበሩት ቁጥቡ ዮናስ ናቸው። ዮናስ ዝምተኛ እና ቁጡ መስለው ቢታዩም ስለ ስነጽሁፍ የነበራቸው እውቀት፣ ለግጥም የነበራቸው ቅናት የትንኔዎቻቸው ምጥቀት እና የቋንቋቸው ለዛ ሌላ ነበር። ይኸ የፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ ዲስኩር በተለይ ስለ ሕትመት ሒደቱ ብዙ ይናገራል። ሸገር ትሪቢዩን ሊደመጥ የሚገባው ነው ብሎ በማመን አቅርቦታል።